Sunday, October 19, 2014

ኦሮሞ እና እስልምና በ“ሕዳሴ አብዮት” መስመር ፪

(ተመስገን ደሳለኝ)
ባለፈው ሳምንት ይህንን ርዕሰ-ጉዳይ፣ በተለይም ኦሮምኛ ተናጋሪው የሚያነሳቸውን አግባብነት ያለው ቅሬታና የተንሸዋረረ የታሪክ ትንተና በተመለከተ በጨረፍታ ዳስሰን ስናበቃ፣ ከእስልምና ጋር የሚያያዘውን ክፍል ጨምሮ ጥቅል የመፍትሔ ሃሳብ መነሻን ለዛሬ በይደር አቆይተነው እንደነበረ ይታወሳል፡፡ እነሆም ተከታዩን እንዲህ እንቀጥላለን፡፡
የእስልምና ጥያቄ
በኢትዮጵያችን የረዥም ዘመን ታሪክ በተለያዩ ከባቢዎች ከተከሰቱት ጭቆናዎች እና የማንነት ጭፍለቃዎች ባሻገር፣ የእስልምና እምነት ተከታዮች የተፈፀመባቸው ሥርዓታዊ በደሎችና ጭካኔዎች፣ አንዳንዴም ጅምላ ጭፍጨፋንም ሳይቀር እንደሚጨምር በደም የተጻፉት ትርክቶች ያስረግጣሉ፡፡ የነገሥታቱ የሥልጣን እርካብ በ‹‹ስዩመ-እግዚአብሔር›› ላይ የተደላደለ በመሆኑ፣ ከኦርቶዶክስ ተዋህዶ ክርስትና በቀር ሌሎች እምነቶች በመዓት-አይን (በጠላትነት) ይታዩ ዘንድ መግፍኤ እንደነበረ ‹‹ዜና መዋዕል››ዎቻቸውን ብቻ በመመርመር መረዳቱ አያዳግትም (በኦርቶዶክስ በሚበየኑት ቅባት እና የፀጋ ልጅ ተከታዮች ላይ የደረሰባቸውን ዘግናኝ እልቂት እዚህ ጋ ማስታወስ ይቻላል)፡፡ በ14ኛው ክፍለ-ዘመን መጀመሪያ ጦረኛው አምደፅዮን ወደዙፋን ከመጣበት ጊዜ አንስቶ እስከ አፄ ዮሐንስ 4ኛ ድረስ እስልምና ላይ የደረሰው ጭፍለቃ አልፎ አልፎ በሠይፍ የታገዘ የግዴታ ጠመቃንም ስለማካተቱ ድርሳናቱ ያወሳሉ፡፡ ፕ/ር ባሕሩ ዘውዴ የአፄ ዮሐንስን የ1871 ዓ.ም የቦሩ-ሜዳ ውሳኔን ተከትሎ የወሎ ሙስሊም ቀን ቀን ‹‹እግዚአብሔር››፣ ማታ ማታ ደግሞ ‹‹አላህ›› ለማለት መገደዱን ‹‹የኢትዮጵያ ሕዝብ ታሪክ›› በሚለው መጽሐፋቸው ማብራራታቸውም የሙግቱን አውድ ያጠናክረዋል፡፡ ዜና መዋዕሎቹም በእምነቱ ተከታዮች ላይ የደረሰውን እንዲህ አይነቱን ሥርዓታዊ የኃይማኖት ጥቃት፣ ማገለል፣ የማምለክ ነፃነትን መገፈፍ እና መሰል የጭካኔ ድርጊቶችን ነገሥታቱ ለአገራቸው የፈፀሙት ውለታ እና አኩሪ ተጋድሎ እንደሆነ በድፍረት መተረካቸው ማሳያ ተደርጎ ሊወስድ ይችላል፡፡
በጥቅሉ በዘመኑ ሥልጣንን ቅቡል ለማድረግ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ድጋፍ ግድ ከማለቱ በተጨማሪ፣ ነገሥታቱ ለክርስትና ያላቸው መታመን እና የሥርዓቱ መተዳደሪያ ሕግ ፍትሐ-ነገሥት መሆኑ ለእስልምና መጨፍለቅ እንደዋነኛ ምክንያት ይጠቀሳል፡፡ የዚህ ውጤት ደግሞ የዛሬውን ‹‹ኢትዮጵያ የክርስቲያን ደሴት ነች›› አይነት ስሁት ፖለቲካ አምኖ የሚቀበል ወንድም-እህት መፍጠሩ አንሶ፣ አንዱ ክፍል ራሱን ‹‹ዜጋ››፣ ሌላውን ‹‹እንግዳ›› አድርጎ ወደማየቱ ጠርዝ ገፍቶታል፡፡ እውነት እንነጋገር ከተባለ ክርስትናም ሆነ እስልምና እትብታቸው የተቀበረው በመካከለኛው ምስራቅ አገራት እንጂ አክሱም አሊያም ሐረር ውስጥ አለመሆኑ ግልፅ ነው፡፡ ግና፣ ቀድሞ ወደሀገር የገባው የበላይ፤ ተከታዩ ደግሞ የበታች እንዲሆን የሚያስገድድ አንዳችም አመክንዮ ማቅረብ በማይቻልበት በዚህ ስልጡን ጊዜም ሳይቀር ሙግቱ አልፎ አልፎ ሲነሳ እየተሰማ በመሆኑ፣ በ‹‹ሕዳሴው አብዮታ››ችን በግንባር ቀደምትነት ፈውስ ሊያገኝ ይገባል ብዬ የማስበው ጉዳይ ሆኗል፡፡
በ1966ቱ አብዮት ንጉሣዊው አገዛዝ ለመጨረሻ ጊዜ ተንኮታኩቶ ከወደቀ ወዲህ መንግስት እና ኃይማኖት በአዋጅ መለያየታቸው ቢደነገግም፤ ግራ-ዘመሙ ወታደራዊው አስተዳደር በስውር ክንዱ ሁሉንም የእምነት ተቋማት ለመቆጣጠር በነበረው ህልም፣ በመንፈሳውያን መሪዎች ላይ አያሌ መከራ ስለማድረሱም ሆነ ተቋማቱን አቅም-አልባ ስለማድረጉ በህይወት ያሉ የዓይን ምስክሮች እልፍ አእላፍ እንደሆኑ ይታወቃል፡፡
ደርግን በ1983 ዓ.ም ወርሃ-ግንቦት ከቤተ-መንግስት አባርሮ በእግሩ የተተካው አብዮታዊ ግንባሩ መጀመሪያ አካባቢ በተለይም የእስልምና እምነት ተከታዮች በአንፃራዊነት ከቀድሞ በተሻለ መልኩ መብቶቻቸው እንዲከበሩላቸው አድርጎ እንደነበረ ይታወሳል (ሥርዓቱ ይህንን መብት የፈቀደ የመሰለው፣ በዋናነት ለመጨፍለቅ ያሰበው የኢትዮጵያ ብሔርተኝነት አንዱ ወካይ የኦርቶዶክስ ኃይማኖት በመሆኑ፣ በ66ቱ አብዮት ያበቃለትን የእምነቱ የበላይነት አለቅጥ በማጎን እና ከመቶ ዓመታት በፊት የተከሰቱ ታሪካዊ ስህተቶችን በማስጮህ ለማድቀቅ የሄደበት ርቀት እንደነበረ ጉዳዩን ያጠኑ ምሁራን ይከራከራሉ) ለዚህም ነው በዘመነ-ኢህአዴግ የኃይማኖት ነፃነት ከአፋዊነት አልፎ በተግባር ሊረጋገጥ ያልቻለው፡፡ ጣልቃ ገብነቱም ለኦርቶዶክስ ክርስትና ‹‹ፓትርያርክ›› እስከ መሾም፣ መጅሊሱም የካድሬዎች መፈንጪያ እንዲሆን እስከማስገደድ ድረስ ለመዳፈሩ የሁለቱም እምነት ተከታዮች የተቃውሞ ድምፅ ዛሬም ተግ አለማለቱ አስረጅ ነው፡፡ ከ2004 ዓ.ም ወርሃ-
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ
2
ታሕሳስ አንስቶ ሕዝበ-ሙስሊሙ በመላ አገሪቱ እያደረገው ያለው ሰላማዊ፣ ነገር ግን ጠንካራና የተደራጀ የተቃውሞ ንቅናቄም ይህንን ሁነት ፍንትው አድርጎ ያሳያል ብዬ አምናለሁ፡፡
በነገራችን ላይ ለረዥም ጊዜ በመካሄድ ላይ ያለው የሕዝበ-ሙስሊሙ ‹ድምፃችን ይሰማ› እንቅስቃሴን በተመለከተ፣ ሌሎች እስካሁን ያሳዩት ዝምታ ምን ያህል አሳሳቢ እንደሆነ እዚህ ጋ ሊነሳ የሚገባው ዓብይ ጉዳይ ነው፡፡ መእምናኑ ለመፍትሔ አፈላላጊነት የወከሏቸው የኮሚቴ አባላት ለግፍ እስር ከመዳረጋቸው በተጨማሪ፤ የእምነት ነፃነት መብቶቻቸው እንዲከበር እና ታሳሪዎቹ መንፈሳውያን እንዲፈቱ በሠላማዊ መንገድ መጠየቃቸው እንደ ወንጀል ተቆጥሮ፣ ‹‹ፀጥታ›› አስከባሪዎች የተከበረው ቤተ-አምልኮ ቅጥር ግቢ ውስጥ ሳይቀር በድፍረት ሰተት ብለው በመግባት እየወሰዱት ያለው ዘግናኝ የኃይል እርምጃ እና ተደጋጋሚ ጭካኔ የተሞላበት ድብደባ፣ እስር፣ እንግልት… የማናችንንም ልብ የሚሰብር ቢሆንም፣ አስፈሪው ዝምታችንን ግን ሊገራው አለመቻሉ እጅጉን ግራ አጋቢ ነው፡፡
ባለፈው ሳምንት በአንዋር መስጊድ የተፈፀመው ኢ-ሰብአዊ ድርጊት (የንቅናቄው አራማጆች ‹‹ጥቁር ሽብር›› ብለውታል) ያለአንዳች የኃይማኖት እና የብሔር ልዩነት ከሕዝበ-ሙስሊሙ ጎን መቆምን አማራጭ አልባ ማድረጉን አምኖ መቀበሉ ከዘገየ ፀፀት ይታደጋል፡፡ በተለይም በሀገሪቱ ፖለቲካ የዳበረ የተሳታፊነት ልምድ ያላቸው የኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታዮች ለዘብተኝነት ያበቃ ዘንድ ወቅቱ ግድ ማለቱን ማስተዋል ብልህነት ነው (በርግጥ የተቃውሞ እንቅስቃሴው በመስጊድ ብቻ መገደቡ ለትብብሩ አንድ እንቅፋት መሆኑን አልዘነጋሁም)፡፡ እዚህ አስፈሪ ‹‹የነርሱ ጉዳይ ነው›› አይነት ገለልተኛ አቋም ላይ ለመድረሳቸው ገፊ-ምክንያት ተብሎ የሚታመነው፣ በፕ/ር ሀጋይ ኤርሊክ ‹የግራኝ ስጋት› (Syndrome) በሚል የተገለፀው አደንዛዥ ስነ-ልቦና ሊሆን እንደሚችል ይገመታል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ክርስቲያኖች አህመድ ኢብን አልጋዚ የሄደበትን የፖለቲካ ስልጣን ፍለጋ አውዳሚ የጦርነት መንገድ፤ በክርስትና መቃብር ላይ የእስልምናን የበላይነት ለማንበር እንደተሞከረ ተደርጎ ለሚቀርበው መላምት መታመናቸው ወደዚህ ጠርዝ የገፋቸው ይመስለኛል፡፡ ይህንን መሰሉ አካሄድም በማኪያቬሊያዊ አስተምህሮ የተዋቀረውን ሥርዓት ዕድሜ ከማራዘም በቀር ቅንጣት ፋይዳ የሌለው በመሆኑ፣ ስጋቱን አራግፎ መጣል አገሪቱን ወደፊት ለመውሰድ ወሳኝ ሚና ይኖረዋል (በአልነጃሺ/አርማህ መሀከል ያለውን የሚታረቅ የማይመስል ቅራኔ ሳንዘነጋ)፡፡ እየተነጋገርንበት ባለው የ‹‹ሕዳሴ አብዮት›› ሀቲት፣ ሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ላይ ቆመን፣ ከአራት መቶ ዓመታት በፊት በተከሰተ (ሊያውም ስምምነት ላይ ሊያደርሱ ያልቻሉ ትርክቶች ባሉበት ሁነት) ይህን ዘመን መቃኘት ረብ የለሽ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ ወደፊት ለመራመድ የክርስቲያኑ ቀዳሚ የቤት ስራ መሆን ያለበት፣ በሕዳሴው የምትፀነሰው ኢትዮጵያ ከሙስሊም ጋር በብቻነት መዋረስ እንደሌለባት ሁሉ፤ እስከአሁን እንደተሸከመቻቸው የሚታሰቡትን ኦርቶዶክስ ቀመስ ትዕምርታዊ እሴቶችንም ለመግራት መፍቀድን ይጠይቃል፡፡
ከእስልምና ልሂቃን አንዱ ኡስታዝ ሀሰን ታጁ፣ ለዚህ አይነቱ አንድነት የሚያግዙ ሦስት ነጥቦችን ያነሳል፡፡ ‹‹ሰይፉን ፍለጋ›› በሚል ርዕስ በቅርቡ ባሳተመው ድርሳኑ፣ ሙስሊም በቀደሙ ጊዜያት በኦርቶዶክስ በዓላት ላይ የመሳተፍ የግዴታ ቀንበሩን መጣሉ አለመቻቻል ተደርጎ መቅረብ እንደሌለበት በአንደኝነት ይጠቅሳል፡፡ ከዚሁ ጋር አያይዞ፣ ባለፉት ሁለት አስርታት የተመለከትነውን የእምነቱ ተከታዩን ‹‹እስልምናን ወደ ማፅደቅ›› መመለስ እንዳለመቻቻል፤ አልያም ሌላ ድብቅ ዓላማ እንዳለው በማስመሰል በጥርጣሬ ማየቱ አደገኛ ስለመሆኑ አጽንኦት ሰጥቶበታል፡፡ ‹‹…‹ቴዎድሮስ ጨፍጭፎናል፣ ዮሐንስ አርዶናል፣ ዘርአያዕቆብ እምነታችንን አንቋሽሿል›… መሰል የታሪክ እውነቶችን መካድ የትም አያደርሰንም›› ሲልም ያስታውሳል፡፡ እነዚህን የኡስታዙ ምክረ-ሐሳቦች የጠቀስኩት፣ ቢያንስ የታሪክ ተዋስኦ ላይ የተፃረሩ ሙግቶች የሚቀርቡባቸውን ኩነቶች ትተን፣ በሕዳሴቷ ኢትዮጵያ በሚበጀው ብያኔ ውስጥ ሙስሊሙን ለመቀላቀል በእጅጉ እንደሚጠቅመን ከልብ በማመን ነው፡፡
ሌላው መሰረታዊ ጥያቄ ደግሞ፣ ከሕዝበ-ሙስሊሙስ ምን ይጠበቃል? የሚለው ነው፡፡ እንደ ሐሰን ታጁ ትንተና አንዱ አስፈላጊ ጉዳይ፣ ኃይማኖቱም ሆነ ተከታዮቹ በተለይም በዘመናዊቷ ኢትዮጵያ መሪዎች ተረግጠው መቀጥቀጣቸው የማይስተባበል ሀቅ ቢሆንም፣ ባለፉት የታሪክ ሁነቶች ላይ ተመስርቶ ጦር መወራወርን ትተው ወደፊት በሚወስዱን ጭብጦች ዙሪያ ለመነጋገር ከመፍቀድና ከመድፈር ውጪ የቀረ ምርጫ አለመኖሩን መገንዘብ እንዳለባቸው ነው፡፡ የሆነው ሁሉ የተነገረውን ያህል ቢሆንም/ባይሆንም፣ አሁን ያለንበትም ሆነ የነገ ዕጣ ፈንታችን በማይበጠሱ ክሮች መገመዱን ተቀብሎ በሕብረት መነሳት ወደመታደሳችን የሚያደርሰን ብቸኛው መንገድ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ኡስታዝ ሐሰን ከላይ ባወሳሁት መጽሀፉ፤ ዶ/ር እንድሪስ ሙሐሙድ ለፒኤችዲ ካዘጋጀው የጥናት ጽሑፍ ላይ የጠቀሰውም ይህንን ሐቅ በሚገባ ያጠናክረዋል፡-
‹‹የአሁኑ ትውልድ ላለፉ ግፎች እና መድሎዎች እውቅና በመስጠቱ በአስተሳሰቡም ሆነ በተግባር የማስተካከያ እርምጃዎችን መውሰድ፤ እንዲሁም ጥላቻን ዘርቶ ከማብቀል መታቀብ ይኖርበታል፡፡ በታሪካዊ ጭቆናዎች ምክንያት የተፈጠሩ ማሕበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ባሕላዊ መበላለጦች የሚካሱበት መንገድም ሊኖር ይገባል፡፡ ምናልባትም በንዲህ አይነት ልባዊ ጥረቶች ያለፉ ቁስሎች ሊሻሩና መጪው ዘመን ጤናማነቱ ሊረጋገጥ ይችል ይሆናል፡፡ ከዚህ ውጪ እውነታውን በመድፈቅና በማድበስበስ ጤናማና ጠንካራ ማሕበረሰብ መገንባት አንችልም፡፡›› (ገፅ 388)
3
ዛሬ በአሰቃቂው ቅሊንጦ እስር ቤት የሚገኘው የመፍትሔ አፈላላጊው ኮሚቴ አባል አሕመዲን ጀበልም ‹‹ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ከ615-1700 የጭቆናና የትግል ታሪክ›› በሚል ርዕስ በ2003 ዓ.ም ለንባብ ባበቃው ቅጽ አንድ መጽሐፉ መግቢያ ላይ የታሪክን ፋይዳ እንዲህ ሲል ገልፆታል፡-
‹‹ታሪክ ትናንትን ለማወቅ፣ ዛሬን ለመረዳትና ለነገ ለማቀድ ያግዛል፡፡ ታሪክ ያለው ሕዝብ በአግባቡ ከተጠቀመበት ታሪክ ይሰራል፡፡ ወደፊት መጓዝ የፈለገ መጀመሪያ ወደኋላ ተመልሶ ታሪኩን ይፈትሻል፡፡ የአባቶቹንና የአያቶቹን ገድል ሲረዳ በምን ሁኔታ ውስጥ እንዳለፉ ግልጽ ብሎ ይታየዋል፡፡ የዛሬው እርሱነቱ የበርካታ ሂደቶች ውጤት መሆኑን ይረዳል፡፡ የአባቶቹንም ስህተት አይደግምም፡፡ የነርሱ ጠንካራ ተሞክሮ ኃይል ይሆነዋል፡፡›› (ገፅ 19)
አብዱልከሪም ታጁ ባለፈው ሳምንት በዚሁ በ‹‹ፋክት›› መጽሔት ላይ ‹‹ወደጥንቱ መመለስ!?›› በሚል ርዕስ ላስነበበን ጽሑፍ መደምደሚያ ያደረገውን ሃሳብ ማከልም ሙግቱን ያጠነክረዋል፡-
‹‹የነ እማሆይ ወተት፣ የነ ሲቲ መይሙና አገር፡፡ የነ የኔታ፣ የነ አብዋ፣ የነ አባዬ፣ የነ ጌትዬ፣ የነ አባ ገዳ አገር፡፡ የነ አብርኸት (የመጀመሪያው ኢትዮጲያዊት ሙስሊም)፣ የነ ድል ወንበራ፣ የነ ምንትዋብ፣ የነ እትዬ ጣይቱ፣ የነ እትዬ መነን አገር፡፡ የነ ኢዛና፣ የነ ነጃሺ፣ የነ ፋሲለደስ፣ የነ አባ ጂፋር፣ የነ ሐሰን አንጃሞ… አገር፡፡ የክርስትና፣ የእስልምና፣ የዋቄፈታና የሌሎች ባሕላዊ ኃይማኖቶች ሀገር፡፡ እነዚህ ሁሉ ናቸው እንግዲህ ማንነታችን የተገመደባቸው ልዩ፣ ጠንካራና ቀለመ-ብዙ ክሮች፡፡ ባሕላችን የተሸመነባቸው ድርና ማጎች፡፡››
…በኢሕአዴግ ስር ያለፍናቸው ዓመታት እንዳስረገጡት ጭቆናው ሙስሊሙን ለይቶ የተተገበረ ካለመሆኑ አኳያ፣ በመጪው የ‹‹ሕዳሴ አብዮት›› ኢትዮጵያን ከውድቀት ለማዳን ወደ መሀከለኛው ፖለቲካ መምጣት በእጅጉ አስፈላጊ ነው፡፡ ለዚህም ሕዝበ-ሙስሊሙ (ልክ እንደ ኦሮምኛ ተናጋሪው ሁሉ) ቀዳሚው አዋጪ መሆን የሚኖርበት፣ ኢሕአዴግ ላይ በእምነትና በጥርጣሬ መካከል ሲዋልል የከረመበት አካሄድ አሁን እንዳየነው ኃይማኖቱን በመጨፍለቅ መደምደሙን በግላጭ መመልከቱ ነው፡፡ የክሽፈቱ ሂደት የሚነግረን አንድ እውነትም፣ መምጣቱ አይቀሬ ነው ብለን በምንከራከርለት የመታደስ አብዮት ይህ የማሕበረሰብ ክፍል ከፊት ለመሰለፍ ካንገራገረ፣ ወደ ጨፍላቂነት ሊያፈገፍግ የሚችል ሥርዓት የሚመጣበትን ዕድል ዳግም መፍቀድ እንደሆነ መገንዘብ እንደሚያሻው ነው፡፡
ፖለቲካው የዘነጋው ማሕበረሰብ
አንድ ማሕበረሰብ በደምም ሆነ በስምምነት መገንባቱን የዓለም ታሪክ ይናገራል፡፡ ግንባታው በደም በተቀባ ታሪክ መካከል የማለፉ አጋጣሚም በራሱ አገሪቱን ባቢሎን ለማስባል ምክንያት አይሆንም፡፡ ‹ይሁን› ከተባለ ግን ኢትዮጵያን በዓለማችን ብቸኛዋ አገር ልናደርጋት እንገደዳለን፡፡ ቀደምት አባቶች ማሕበረሰብን ለዘለዓለም በአንድነት ለማፅናት ከጠብ-መንጃ በተጨማሪ ቋንቋ፣ ባሕል፣ መልከዓ-ምድርና መሰል ጉዳዮችን ለማስተሳሰር ይሞክሩ እንደነበረ ይታወሳል፤ ብዙውን ጊዜም ከሰላማዊው ስምምነት ይልቅ፣ በኃይል ማስገበርን ይመርጡ ነበር፡፡ በኢትዮጵያችን ይህ መንገድ ካስገኘው ትልቁ ውጤት በተቃርኖ፣ ታሪክን ዘመኑን የመበየኛ ‹‹ፖለቲካ›› በማስመሰል የልዩነት በርን ለማስፋት ለሚሞክሩ ሥልጣንን የሚያሰሉ ኃይሎች የመጫወቻ ካርድ ሆኖ እያገለገለ ነው፡፡ ግና፣ እነስፓርታና ትሮይ በኃይል መገበራቸው የዛሬዋን ሄለናዊ ግሪክ መፍጠር መቻሉን እንጂ፤ በዚህ ዘመን መነፅር ተቃኝቶና ለብይን ቀርቦ የ‹‹እንገነጠላለን›› ጥያቄ ስለማስነሳቱ ተሰምቶ አይታወቅም፡፡ የአገርን የመጨረሻ ቅርፅ ያበጁ ማሕበረሰባዊ ውሎች ከፖለቲካዊ ፍቺ ይልቅ፣ አንድነትን ለማፅናት ያላቸውን አስተዋፅኦ ያህል፣ ሂደቱ የዜጎችን እልቂት፣ የማንነት ጭፍለቃን፣ የኃይማኖት ድፍጠጣን፣ የባሕል ወረራን… የማድረሱን አይቀሬነትም በቅንነት መረዳትን ይጠይቃል፤ ሙግቱም ከዚህ አውድ ሊርቅ አይገባውም፡፡
ፖለቲካዊ ውሳኔዎች ማሕበረሰባዊ እሴቶችን ዘንግተው ጊዜያዊ ትርፍን ብቻ ታሳቢ ካደረጉ ከትውልድ ትውልድ በቀላሉ የማይቋጭ ከባድ የቤት ስራ ሰጥቶ የሚያልፍ ጠባሳ መተዋቸው አከራካሪ አይደለም፡፡ ይህም ሆኖ በኦሮሚያ ከማንነት ጭፍለቃ፣ በታሪክ ከመዘንጋት እና የፌዴራሊዝም ሥርዓቱ በትክክል ካለመተግበሩ ጋር የተያያዙ ጥያቄዎችን ተከትሎ፣ ዝነኛው የቃሊቲ ማጎሪያ ለቋንቋው ተናጋሪ ወጣቶች ሌላኛው የሲኦል ቤት የሆነበትን ኩነት ማስተባበል አይቻልም፡፡ የብሔሩ ልሂቃን ባላጠሩት ወይም በከፋፈሏቸው መሰረታዊ ልዩነቶች መንስኤነት ወክለነዋል የሚሉት ማሕበረሰብ የስቃዩ ገፈት ቀማሽ እንዲሆን መግፋታቸውን ሳንዘነጋ ማለት ነው፡፡ በርግጥ ወደዚህ ድምዳሜ የሚያደርሰን ‹ጥያቄዎቹ ከመገንጠል በመለስ ሁነኛ ምላሽ የላቸውም› የሚሉትን ያህል፤ ‹ስርየቱ ዲሞክራሲያዊ አንድነት ብቻ ነው› የሚሉ፤ አሊያም ሀገሪቱን እስከወዲያኛው በብቸኝነት በመግዛት ዙሪያ የሚያጠነጥኑ ኃይሎች በአንድ ብሔር ጥያቄ አፈታት ላይ የተያዙ አቋሞች የመሆናቸው እውነታ ነው፡፡ ከእነዚህ ፖለቲካዊ ምላሾች መካከል መገንጠል ወይም በብቸኝነት የሥልጣን ይገባኛል ጥያቄ ተግባራዊ የሚሆንበት አጋጣሚ ቢፈጠር፣ የሀገር ህልውናን የተሸከሙ አዕማዶች ፈራርሰው፤ ዘመናትን የተሻገረው ማሕበራዊ ትስስር ተበጣጥሶ አገር-አልባ የተበታተነ ትውልድ መውለዳቸው አይቀርም፡፡ ኦሮሚያን ከተቀረው የአገሪቱ አካል መገንጠል፣ ዛሬም ክልሉ በተዋቀረበት መልከዓ-ምድራዊ ቅርፅ ውስጥ ሌሎች ህዳጣኖችን ማስተናገድ የሚያስችል ሥርዓት ማበጀት እንደማይቻል (በብሔር ፌደራሊዝሙ ትግበራ ያየናቸው ጉድለቶች እንደማይከሰቱ ተገንጣይ ልሂቃኑ በቂ
4
መከራከሪያ እንኳ ሲያቀርቡ አልሰማንም) እና የተዳፈኑ ሌሎች ጥያቄዎች ፈንቅለው ከመውጣትም ሆነ በማያቋርጡ አዳዲስ ችግሮች የቋንቋውን ተናጋሪ ከመናጥ አይታደግም፡፡ በብቸኝነት የመግዛት ጥያቄም ቢሆን (ኦሮሞ ብዙ ከመሆኑ አኳያ ሁሉም የቋንቋ ተጋሪውን ልሂቅ ብቻ ይመረጣል ከሚል ምክንያተ-አልቦ መነሻነት) የበላይ ልሁን ባይነትና ኢ-ዲሞክራሲያዊ ከመሆኑም ባሻገር የዘመኑን መንፈስ የሚፃረር ነው፡፡
ወደድንም ጠላን ኦሮምኛ ተናጋሪው እንደከዚህ ቀደሙ የልሂቃኑን ያልተፈተነ ፖለቲካዊ የመፍትሔ ሃሳብ ብቻ አንጠልጥሎ፣ ከወንድምና እህቶቹ ጋር ለዘመናት የገነባውን ሁለንተናዊ ትስስር ጥሎ እንዲነጉዱ የሚገፉበት እኩይ ቀመር የሚያከትምበት ጊዜ ላይ ደርሰናል፡፡ ስለምን ቢሉ? ያለፈው ታሪካችን በደም መገንባቱ ባይካድም፣ ዛሬም ዕጣ-ፈንታችን በዚህ ሊደመደም አይቻለውምና ነው፡፡ እነዚህን ችግሮችም በማያዳግም ሁኔታ ለመፍታት፣ በቀዳሚነት ኦሮምኛ ተናጋሪው ክፍል እና የአንድ ጠቅላይ ኢትዮጵያ አቀንቃኝ ሆነው የምናገኛቸው ወገኖቻችን መካከለኛውን የመቻቻል መደላድልን ለመፍጠር በሰጥቶ መቀበል መርህ የተቃኘ መፍትሄን አምነው የመተግበር ተነሳሽነት ሊኖራቸው እንደሚገባ አምናለሁ፡፡ ዶ/ር መረራ ጉዲና ‹‹የኢትዮጵያ ፖለቲካ ምስቅልቅል ጉዞና የሕይወቴ ትዝታዎች›› በሚል ርዕስ ባሳተሙት መጽሐፍ ይህንን መንገድ መከተሉ አዋጭ እንደሆነ የገለፁት እንዲህ ሲሉ ነው፡-
‹‹ብዙዎቹ የዛሬ 30 እና 40 አመታት ብቻ ሳይሆን፣ የዛሬ 130 እና 140 አመታት በፊት የነበረውን ጭምር የታሪክ ሂሳብ እንተሳሰብ የሚሉ ይመስሉኛል፡፡ የኦሮሞ ልሂቃን ዋና ችግራቸው የጋራ የፖለቲካ አጀንዳ ለመቅረፅ ከመጣር ይልቅ ለብቻቸው የሚደረገው ትግልን የመንግስት ሰማያት አስተማማኝ መንገድ አድርገው ማምለካቸው ነው፡፡ የአማራው ልሂቅ ዋና በሽታው በዋናነት በአማራ ልሂቃን የተፈጠረች የዛሬይቱ ኢትዮጵያ እንደዛው ትቀጥል ነው፡፡ እምነታቸው መቀጠልም ትችላለች ነው፡፡ ባለፉት አርባ ዓመታት የሀገሪቱ ፖለቲካ ዋናው ቀውስ ምንጭም እንደነበረች መቀጠል ያለመቻሏ መሆኑን በውል መገንዘብ ያቃታቸው ይመስለኛል፡፡›› (ገፅ 261-262)
የ‹‹ሕዳሴው አብዮታ››ችን ዋነኛ ግብም በዴሞክራሲያዊ አንድነት የፀናች፣ የጠነከረችና የታደሰች ኢትዮጵያን መፍጠር እንጂ፣ በቀላሉ ሊታረቁ በሚችሉ ልዩነቶቻችን ላይ እሳት ለኩሶ የመበጣጠስን አደጋ መጋረጥ አለመሆኑን ማስታወሱ አስፈላጊ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ ሌሎች የዓለም አገራትም ይህን መሰሉን የብሔር ጥያቄ (ቅራኔ)፣ ያለደም መፋሰስና መበታተን የተሻገሩበትን ጥበብ ብንፈትሸው እውነተኛ ዲሞክራሲን በማስፈን እንደነበረ እንረዳለን፡፡ ‹ከቡድን መብት ውጪ ሌላ ነገር አያሳየኝ› የሚል ግትር አቋም ይዞ የሚንገታገተው ኢህአዴግን ጨምሮ በተአማኒ ምርጫ ለሥልጣን የሚወዳደሩ ሁሉም የፖለቲካ ድርጅቶች፣ በ‹‹ሕዳሴ አብዮት›› ግለሰብን-እንደግለሰብ እውቅና እንዲሰጡ የመገደዳቸው እውነታም ሆነ በዲሞክራሲያዊው መንገድ የሚመሰረተው ሥርዓት በኦሮሚያ ብቻ ሳይሆን በየትኛውም የአገሪቱ ክልል የሚነሱ መሰረታዊ ጥያቄዎችን በብቃት የመመለስ አቅም እንዲኖረን የሚያስችለው መተማመኛችን ያሳለፍናቸው የመከራ እና የልዩነት ዓመታት ሁነኛ ተሞክሮዎች በመሆናቸው ነው፡፡
የ‹‹ሕዳሴ አብዮት›› ተዋስኦ
በተከታታይ ክፍሎች የተነጋገርንበት የ‹‹ሕዳሴ አብዮት›› በጠንካራ ትውልዳዊ መሰረት ይገነባ ዘንድ፤ በተነሱት ሃሳቦች ዙሪያም ሆነ ተለጣጭ ርዕሰ-ጉዳዮች ላይ አሀዱ የሚባሉ የአደባባይ ውይይቶች በእጅጉ አስፈላጊ እንደሆኑ መዘንጋት የለበትም፡፡ ይህም የአብዮቱ ተግባሮት ቀዳሚ ጅማሮ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ የሀገራችንን ሁለንተናዊ ገጾች በማደስ ይበየናል የምለው የሕዳሴው አብዮት፣ ካለምሁራዊ ተዋስኦ የምንፈልጋትን ከራሷ ጋር የታረቀች ኢትዮጵያን እንደማያመጣልን አምናለሁ፡፡ የመንግስታችንም ሥርዓት በዘውግ ተኮር ልባሶች የሚቀነቀኑ ፖለቲካዊ ግቦችን የማዘል አዝማሚያ እንዳለው እረዳለሁ፡፡ ይህም፣ ማሕበረሰባችንን ለተሻለ የፖለቲካ ሥርዓት ግንባታ ከማሳተፍ ይልቅ፣ ወደኋላ እንዲንሸራተት አስተዋፅኦ ማድረጉ ግልፅ ነው፡፡ የሚመጣው አብዮት፣ የኢትዮጵያን የቁልቁለት ጉዞ በመግታት፣ እንደሀገር መቀጠል እንድትችል ብቻ ሳይሆን፣ ሁሉንም ፍላጎቶች የሚያካትት ይሆን ዘንድ፣ በዚህ መንፈስ የተቃኘ የአደባባይ ሙግት አይነተኛ ሚና ይኖረዋል፡፡ በተዋስኦ ጅማሮም፣ ክብደት ልንሰጣቸው የሚገቡትን ጭብጦች ከዚህ ቀደም በሕዳሴ መምህርነት ከጠቀስኳቸው ልሂቃን ክርክሮች መነሳት የሚቻል ይመስለኛል፡፡ የመስፍን ወልደማሪያምን የክሽፈት ኃልዮት ማሕበረ-ባሕላዊ እና ሥርዓታዊ ምንጮች መፈተሽና ማብራራት፤ የመሳይ ከበደን የሀገሪቷ የቀደሙ ስልጣኔዎች መገታት ለመሻገር ዘመናዊነትን ከልማዳዊ ማንነቶቻችን ጋር በመለንቀጥ እንደገና አቧራውን ማራገፍ ይቻላልንም ሆነ፤ የተከሰተ ነጋሽን የትምህርት ሥርዓታችንን በሀገረኞቹ አማርኛ እና ኦሮምኛ ቋንቋዎች ሙሉ ለሙሉ መቀየር የሚለውን ሙግት ጨምሮ፣ ከዚህ ቀደም ኦሮሚያን ለመገንጠል ይታትሩ የነበሩት ሌንጮ ለታ በቅርቡ በመሰረቱት ድርጅታቸው (ኦዴግ) ‹‹የፖለቲካ ፕሮግራሜ›› ብለው የዘረዘሯቸው ነጥቦች የመታደሰቸው ምልክት በመሆኑ፤ እንዲሁም የሐሰን ታጁ የመቻቻል ትርጓሜና የአንድነት የመፍትሔ ሃሳብ (በተለይም የታሪክ ወቀሳና ሮሮ ላይ ማተኮሩን ማለዘቡ ከተሳካለት) የሕዳሴው ተዋስኦ አዕማዶች ሊሆኑ የሚችሉ ይመስለኛል፡፡
በዚህ መንፈስ ይገራል ብዬ የምታመንለት ተዋስኦ፣ ከዚህ ጽሑፍ አንፃር የሚያተኩርባቸው ዕሴቶች ይኖሩታል፡፡ በኦሮሞ ጥያቄ እና በሙስሊሙ ጉዳይ ላይ የሚኖረን ክርክር፣ ያለፉትን አሟጋች የታሪክ ኩነቶችንና ሰብዕናዎችን ለአካዳሚው ክበብ
5
በመተው፤ ሁለቱ የማሕበረሰብ ክፍሎች ኢትዮጵያን ዳግም በመበየን እና በአብዮቱ ሊኖራቸው የሚገባ ሚና ዋነኛ መሆን ይኖርበታል፡፡ ከኃይማኖቱም ሆነ ከኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪው ማሕበረሰብ ለሕዳሴው እውናዊነት የሚበጁ የዘነጋናቸውን ዕሴቶችን መመርመር እና እነርሱንም በተዋስኦው ውስጥ አጥብቆ መግፋት፣ አንዱ ቀጣይ የቤት ስራችን ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ …እነሆም በማሕበረሰባዊ ክፍሎች መሀከል ብዙ ፈታኝ አደጋዎችን ተሻግሮ የመጣው ሁለንተናዊ ትስስራችን በአብዮቱ ዳግም ይታደስ ዘንድ፣ የአገሬ ልጆች ነቅተው እንዲጠብቁት በጥብቅ እመክራለሁ፡፡
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!
ኢትዮሚድያ - Ethiomedia.com

No comments:

Post a Comment